Wednesday, May 16, 2012

ነብይ በአገሩ አይከበርም


መቼም በልባችሁ ዛሬስ ደግሞ ሰበካ ጀመረ ሳትል አትቀሩም። ኧረ ከየት ብዬ፡በየትኛው እውቀቴ። የዚህ ጹህፍ ዓላማ ከሰበካ ጋር በጭራሽ ግንኙነት የለውም፡ጥቅሱን የተጠቀምኩበት ባለፈው አስራምስት ቀን ታስቦ የዋለውን የዓለምዓቀፉን የፕሬስ ነጻነት ቀንን ከተሸላሚዎቹ "አሸባሪ" ጋዜጠኞቻችን ጋር ለማነጻጸር ያህል ብቻ ነው የተጠቀምኩበት። ያው እንደምታውቁት የዓለምዓቀፉ የፕሬስ ነጻነት ቀን በፈረንጆቹ ግንቦት ወር መጀመሪያ ላይ በመላው ዓለም ታስቦ የዋለ ሲሆን ኢትዮጵያን የመሳሰሉ በዴሞክራሲያዊነት በጋዜጠኞች አያያዝ እጅግም የማይታሙ አገሮችም ቀኑን በተለያዩ መንገድ አክብረውታል፡አጃኢብ አለ ማን ነበር እሱ። ይህ በእንዲህ እንዳለ፡ በእስር ላይ የሚገኙት አሸባሪ ኢትዮጵያውያን ጋዜጠኞች ማለትም እስክንድር ነጋና ርዕዮት አለሙ ከሁለት የተለያዩ በአሜሪካ የሚገኙ የፕሬስ ነጻነት ተሟጋቾች ለሽልማት አጭተዋቸዋል። ፔን አሜሪካን ማዕከል ጋዜጠኛ/ብሎገር እስክንድር ነጋን የዚህ ዓመት (2012 ዓ᎐ም᎐) የፔን/ባርብራ ጎልድስሚትዝ የመጻፍ ነጻነት አሸናፊ ብሎ የሰየመው ሲሆን፡ ባለቤቱ ሰርካለም ፋሲል ለባለቤቷ የተበረከተውን ሽልማት ሜይ 1/2012 ዓ᎐ም᎐ ኑውዮርክ ከተማ በመገኘት ተቀብላለች። እንደሚታወቀው ሰርካለም የ 1997  ዓ᎐ምን  ምርጫ ተከትሎ በተከሰተው ብጥብጥ ምክንያት ከባለቤቷ ጋር ለ17 ወራት በታሰረችበት ወቅት ልጃችውን ናፍቆት እስክንድርን እንደተገላገለች የምንዘነጋው አይደለም። በጣም የሚገርመው ግን ሰርካለም እንደባለቤቷ ጋዜጠኛ ብቻ ሳትሆን የ 2007ቱ የዓለምዓቀፉ የሴት ጋዜጠኞች ተቋም ጀግና ጋዜጠኛ ተሸላሚ ነች። መቼም ምንይልክ ቤተመንግስት ውስጥ የሚኖሩ መሪዎቻችን እነዚህ አሜሪካኖች አበዱ ወይ ሳይሉ አይቀሩም።
ኧረ ገና ምን ታይቶ፡የእስክንድር ነጋ ሲገርማቸው ይባስ ብለው
በአሸባሪነት ተከሳ 14 ዓመት ተፈርዶባት ዘብጥያ የወረደችውን አምደኛ ርዕዮት አለሙን ሰርካለምን የሸለማት ተቋም እቺን አሸባሪ ደግሞ የዚህ ዓመት ማለትም በፈረንጆቹ የ 2012 ዓ᎐ም᎐ ጀግና ጸሃፊ በማለት መርጧት እርፍ። ይገርማል አቤት እንደ አሜሪካኖች ግን ውለታ አፍራሽ የለም መንግስታችን በመንግስታቸው ትዕዛዝ ከአንዴም ሁለት ጊዜ ሶማልያ ለጦርነት ሄዶ በሺዎች የሚቆጠሩ ወጣት ኢትዮጵያውያንን የገበረውን እና እየገበረ ያለውን ከውለታ በመቁጠር ምናለበት ዋልታ፡ፋና፡ወይን ውስጥ ካሉ እኔ ነኝ ያሉ ልማታዊ ጋዜጠኞቻችን መካከል እንኳን ቢሸልሙ ምን ነውር አለበት። ይሄ ከብዕርና ከኮምፕዊተር ጀርባ ተደብቀው ህገመንግስቱን በሃይል ለመናድ ላይ ታች የሚሉ አሸባሪዎችን ጀግና ጸሃፊ እያሉ መሸለም ነገ በታሪክ ሊያስጠይቅ እንደሚችል ሸላሚዎቹ ሊገነዘቡት ይገባል። 
መቼም ወጉ እንዳይቀር በሽመልስ ከማል
የሚመራው የኮምኒኬሽን መ/ቤትም እለቱን አዎ የዓለምዓቀፍ የፕሬስ ነጻነት ቀንን በደመቀ ሁኔታ ያከበረ ሲሆን፡ስለእነ እስክንድር ነጋና ርዕዮት ዓለሙ መሸለም ዜናው የደረሰው አይመስልም፡፡ እንዴ በየት አድርጎ ይስማ፡ ከኢትዮጵያ ውጭ ያሉ ኢትዮጵያውያን ድረገጾች ታግደው፡በስልክና በኢንተርኔት የሚደረጉ የመልዕክት ልውውጦች እየተጠለፉ ብርሃንና ሰላም ማተሚያ ቤት ጸሃዩ መንግስታችን ከሃያዓንድ ዓመት በፊት ያሰወገደውን ሳንሱር በስራ ላይ እያዋለ በየት አድርጎ የነዚህ አሸባሪ ተብዪ ጋዜጠኞች ሽልማት ዜና እነ ሽመልስ ከማልና በረከት ስምዖን ጆሮ በየት አድርጎ ይድረስ። ልብ ላችሁ ይሄን ምስል ብትመለከቱ ታዳሚዎቹ የህሊና ጸሎት የሚያደርጉ ይመስላል። እንደው ለማን ይሆን፡መቼም ቀብሩ እየተፋጠነ ስላለው የኢትዮጵያ ፕሬስ የምትሉ ካላችሁ ይሄ የጸረ ልማታዊ ጋዜጠኞች አሉባልታ እንጂ ሌላ ሊሆን አይችልም። አቤ ቶኪቻው ስለዚች ታሪካዊ ፎቶ ምን የምትለው አለህ?
በኢትዮጵያ የሚገኙ የውጭ አገር ጋዜጠኞች ማህበር በበኩሉ የዓለምዓቀፉን የፕሬስ ነጻነት አገርቤት የሚገኙና በተለያዩ ጋዜጦችና መጽሄቶች የሚጽፉ ጋዜጠኞችን ላቅ ያለ አገልግሎት መሸለሙን አስመልክቶ በዜና መልክ ከማህበሩ በትዊተር አድራሻዬ የደረሰኝ ሲሆን ስለእነእስክንድርና ርዕዮት ዓለሙ መሸለምም ሆነ ኢትዮጵያ ውስጥ ስላለው የሚድያ ሁኔታ ምንም የተጠቀሰ ነገር ባለመኖሩ የላከልኝን ግለሰብ ለምን ይሄ ሊሆን እንደቻለ ጠየቅኩት። ከጥቂት ደቂቃዎች በኋላ ግለሰቡ ነገሩን በማድበስበስ በዜናው ላይ ስለነእስክንድር መሸለም መጠቀሱን ለማስተባበል ሞከረ እኔስ በመቀጠል በላከልኝ ዜና ላይ ምንም የተጠቀሰ ነገር አለመኖሩን መለስኩለት።
ከዓፍታ በኋላ ብስጭት በተቀላቀለ መልኩ በዝግጅቱ ላይ ነበርክ ብሎ ጠየቀኝ you weren't there were you? We have honored ALL our colleagues that night። በጣም ቀልደኛ ወይም የሌባ ዓይነደረቅ የሚሉት ፈረንጅ መሆን አለበት እስቲ አስቡት እኔ ያለሁት ስዊድን ዝግጅቱ የተካሄደው ከሁለት ቀናት በፊት አዲስ አበባ። እናም በዝግጅቱ ላይማ እንዳልነበርኩ ምንም ጥያቄ የለውም ብዬ መለስኩለት። ይሄ ፈረንጅ ጋዜጠኛ ምን ቢለኝ ጥሩ ነው፡በዝግጅቱ ላይ እነእስክንድር ነጋን እና ርዕዮት ዓለሙን ዘክረናቸዋል ነገርግን በላክነው ዜና ላይ ያልተጠቀሱት ዜናው በዋናነት የሚያተኩረው በዕለቱ ድርጅታችን ስለሸለማቸው የአገር ውስጥ ጋዜጠኞች በመሆኑ ምክንያት ነው press release is abt [about] winners but we had an audience discussion abt [about] and an honorable mention of all our jailed colleagues as well። ካፈርኩ አይመልሰኝ ነው ነገሩ እነእስክንድርና ርዕዮት መሸለም ከላይ በጠቃቀስኳቸው ምክንያቶች አልሰሙ ይሆናል (ስላቅ ሄሄሄ) እንደው ባሸባሪነት ተከሰው ቃሊቲ በእስር ላይ ስለሚገኙት ስውዲናውያን ፈረንጅ ጋዜጠኞች አንድ መስመር አለመጻፍ ግን ያጠያይቃል። እናም ነብያት ማለትም ኢየሱስ/እስክንድር ነጋ/ርዕዮት ዓለሙ/አንዷለም አራጌ/ሌሊሳ ኦልባና ወዘተ በአገራቸው አይከበሩም አሜን። አበቃሁ፡እስቲ ደሞ ትንሽ ልተኛ።   


No comments:

Post a Comment