Sunday, December 18, 2011

"የማስተዳድረው ቆንስላ ሳይሆን የአስከሬን ማቆያ ነው" በሊባኖስ የኢትዮጵያ ቆንስል


ይህንን ጽሁፍ በእንግሊዘኛ የራሴ በሆነች ብሎግ ላይ የጻፍኩት ከጥቂት ሳምንታት በፊት ቢሆንም ወደአማርኛ እንድተረጉመው ያነሳሳኝ በቅርቡ በፍትህ ጋዜጣ ላይ ""ኢትዮጵያዊ ዋጋው ስንት ነው?"" የሚለውን መጣጥፍ ካነበብኩ በኋላ ነው:: እኔ በበኩሌ የእኛ ኢትዮጵያውያን ዋጋ ተንኮታክቶ ወርዶ በዚህ ዘመን ከሌላው የሰው ዘር አይደለም ከምንም አይነት ግዑዝ ነገር በታች እንደሆነ ይሰማኛል:: ኢትዮጵያዊ መሆን አይደለም ለምን እዛች አገር ተፈጠርኩ የሚያሰኝበት ጊዜ ላይ በእርግጠኝነት ደርሰናል:: ዛሬም በገልፍ እና በሜዲትራንያንን ባህሮች ወገኖቻችን የሻርክ ሲሳይ እየሆኑ ነው: ዛሬም ወገኖቻችን በሲናይ በረሀ በበድዊን ጎሳ አባላት ለባርነት ለእስራት ለድብደባ ለአስገድዶ መድፈር እንዲሁም በአሰቃቂ ሁኔታ ህይወታቸው ሳያልፍ እንደ እንሰሳ እየታረዱ የውስጥና የውጭ አካል ክፍሎቻቸው እየተወሰደ ሬሳቸው በየቦታው በመጣል ላይ ይገኛል: ዛሬም እኛም ሆን መሪዎቻችን ይሄ በሰው ልጅ ታሪክ ተሰርቶ የማያውቅ ግፍ በወገኖቻችን ላይ ሲፈጸም ሰምቶ እንዳልሰማ አይቶ እንዳላየ በመሆን ጭንቅላታችንን አሸዋ ውስጥ ቀብረናል:: ከዚህ በላይ ሞት ውርደት ከየት ሊመጣ:: ለዚህ እንደማስረጃነት ደግሞ ሩቅ መሄድ አያሻም: ቦሌ አለማቀፍ አውሮፕላን ማረፊያ በየቀኑ
መካከለኛው ምስራቅ የራሳቸውንና የቤተሰባቸውን ኑሮ ለማሻሻል የሄዱ ሴት እህቶቻችንና ልጆቻችን ሰውነታቸው በአሰቃቂ ሁኔታ ተቆራርጦ/ተበለሻሽቶ እድለኛ የሆኑት ደግሞ ከነሙሉ አካላቸው ሬሳቸውን መቀበል እንደተራ ነገር እየተቆጠረ ከመጣ ቆየት ብሏል:: በሺዎች የሚቆጠሩ ሌሎች እህቶቻችን/ልጆቻችን ዛሬም በእነዚህ የአረብ አገራት በአስሪዎቻቸው ይደበደባሉ:ይንገላታሉ:ተገደው ይደፈራሉ: ይራባሉ:ይጠማሉ:በባርነት ይማቅቃሉ:ባስ ሲልም ይገደላሉ ወይም ራሳቸውን አጠፉ ተብሎ ወደ አገርቤት አስክሬናቸው አይሆኑ ሆኖ ይላካል:: ሌሎች በሺህ የሚቆጠሩ እድለኞቹ እድለኛ ከተባሉ በለበሱት ጨርቅ በእነዚህ አገራት በሚገኙ እስርቤቶች ያለማንም ጠያቂ እና ክስ ሳይመሰረትባቸው ለዐመታት ፍዳቸውን በመግፋት ላይ ይገኛሉ:: በጥቅምት ወር አጋማሽ ላይ እንኳን ሁለት እህቶቻችን በሁለት ተከታታይ ቀናት በኩዌት እና ሊባኖስ ህይወታቸውን አጥተዋል አንደኛዋ በአሰሪዋ በደረሰባት ድብደባ ሲሆን ሌላኛዋ ደግሞ
ራስዋን አጠፋች ተብሎ ምክንያት ተስጥቷል:






ለንጽጽር በማለት በዱባይ የሚገኙት የኢትዮጵያ እና የፊሊፒንስ ኤምበሲዎች ለዜጎቻቸው የሚሰጧቸውን አገልግሎቶች የሚከተለውን ዘጋቢ ፊልም ማየት ብቻ ይበቃል:: የፊሊፒንስ ኤምበሲ ዱባይ በቤት ሰራተኝነት ተቀጥረው በመጡ ዜጎቹ ላይ የሚደረሰውን በደል ለመከላከል እና መብቶቻቸውን ለማስጠበቅ የ24 ሰዐት የሆት ላይን የስልክ አገልግሎት ሲኖረው የኢትዮጵያ ኤምበሲ ደግሞ በአሰሪዎቻቸው የሚፈጸምባቸውን በደል ለማመልከት እና ችግራቸው እንዲፈታላቸው አቤቱታ ይዘው የመጡ እህቶቻችንን ከአገሪቱ ፖሊስ ጋር በመተባበር በእስር እንዲንገላቱ የአገር ዜግነቱን እየተወጣ ይገኛል:: የራሷን እና የቤተሰቦቿን ህይወት ለመለወጥ ወደ ዱባይ ያቀናችው የ23 አመቷ ለጋ ኢትዮጵያዊ እህታችን/ልጃችን ትርንጎ የት እንደገባች እስካሁን የሚያውቅ የለም ወይም ለማወቅ የሚቆረቆር አካል የለም:: ያንን ፊቷ ላይ የሚታይ የዋህነት እና የልጅነት ፈገግታ አይቶ ይሄ በየቀኑ የምንሰማው እና የምናየው አሰቃቂ በደል እንዳይደርስባት መጸለይ ብቻ ሳይሆን መታገልም የዜግነት ግዴታችን ሊሆን ይገባዋል:: በሊባኖስ የሚገኘው የኢትዮጵያ ቆንስላ ሀላፊ ሲ.ኤን.ኤን. ለተባለው የአሜሪካን የቴሌቪዥን ጣቢያ በሰጡት ቃለመጠይቅ ጉዳዩን ጥርት ባለ መልኩ እንደሚከተለው አስቀምጠውታል: "" የምመራው ኤምበሲ ሳይሆን የአስክሬን ማቆያ ነው::'' ከዚህ የበለጠ ምን ውርደት እና መርከስ አለ ወገኖቼ??? አይ ኢትዮጵያ, እንዴት ነው በዲፕሎማት እጥረት የተነሳ አስከሬን ገናዦችን በአምባሳደርነት/ቆንስላነት መላክ ጀመርሽ? የአንድ አምባሳደር ሀላፊነት የሀገሩን ጥቅም ከማስከበር እና ከመማስተዋወቅ ባሻገር ተመድቦ በሚሰራበት ሀገር የሚኖሩ ዜጎችን መብት እና ደህንነት መከታተል ማስከበር እና መብቶቻቸው ሲጣሱም በሀገሪቱ ከሚገኙ የህግ አካላት ጋር በመነጋገር እና በመወያየት ያሉባቸውን ችግሮች እንዲፈቱ ጥረት ማድረግ ግብር ከፋዩ ህብረተስብ ከሚጠብቅበት ሀላፊነቶች አንዱ ነው አለዚያማ በቀጥታ የእህቶቻችንን አስከሬኖች በእነዚሁ አገሮች ከሚገኙ ሆስፒታሎች በቀጥታ መረከብ ወጪ ቆጣቢ ከመሆኑም ባሻገር አገሪቱ ለቆንስላው/ኤምበሲው ኪራይ እና ለሰራተኞቹ ደሞዝ የምታፈሰውን የውጭ ምንዛሪ ለሴት እህቶቻችን አገር ውስጥ ስራ ብትፈጥርበት እኛንም ከውርደት እህቶቻችንንም ካላስፈላጊ ሞት እና እንግልት ""አምባሳደሮቻችንንም""...ብቻ ይቅር:: ጉዳዩ በዚህ ቢያበቃ ጥሩ ነበር እነፊሊፒንስኢንዶኔዢያመንግስታት ከዚሁ ሁሉ ውርደት እና ስቃይ የአረብ ገንዘብ ይቅርብን ብለው ዜጎቻቸውን ለስራ (ባርነት ብለው ይቀላል) ወደ ሳውዲ አረቢያ የሚልኩ ቀጣሪ ድርጅቶችን ማገዳቸው ይታወሳል እድሜ ለኢትዮጵያ የተከበሩ ፕሬዝዳንታችን ለህክምና ሳውዲ ቆይተው ሲመለሱ በሰጡት ጋዜጣዊ መግለጫ ሳውዲዎች በዚህ ጉዳይ ምንም ሀሳብ እንዳይገባቸው እና ኢትዮጵያ በዚህ ረገድ በሺህ የሚቆጠሩ ወጣት ዜጎቿን ለመገበር ቅንጣትም ወደ ኋላ እንደማትል አረጋግጠዋል:: ልብ በሉ ሳውዲ አረቢያ ባለፈው ሰኔ የ54 አመቷን ኢንዶኔዢያዊ አንገቷን በመቅላቷ ትልቅ ተቋውሞ አስነስቶ ኢንዶኔዢያም ዜጎቿ ወደ ዛች አገር ድርሽ እንዳይሉ ከልክላለች:: እነዚህ ምስኪን እህቶቻችንና ልጆቻችን ቢገደሉ ቢራቡ ቢታረዙ ቢጠሙ ቢደበደቡ ጉልበታቸው ቢበዘበዝ አካላቸው በፈላ ውሀ ቢቃጠል በካራ ቢበለት ማን ጉዳዬ ብሎ ኬሬዳሽ አበራሽ ብትሞት ጫልቱ ትተካለች; ዘምዘም አካሏ ቢጎል ሰናይት በሷ ቦታ ትተካለች:: የትም ፍጪው ዶላሩን አምጭው ነገሩ:: ግዜ ካላችሁ www.አረብታይምስ.com የሚለውን ድረገጽ ተመልከቱማ ምን ይመስላችሁዋል ስማቸውን www.abuse-ethiopianhousmaids.com ቢሉት ይበልጥ ከደረገጹ ይዘት ጋር የሚስማማ ይመስለኛል ለምን አትሉም ከደርዘን በላይ የሚሆነው ዜናቸው በየቀኑ በኢትዮጵያውያን እህቶቻችን ስቃይ እና መከራ በመሆኑ ነው:: ምን ያህል ዋጋችን አሽቆልቁሎ መቀመቅ እንደወረደ ከዚህ በላይ ማስረጃ አያስፈልግም: መቼም ከዚህ የበለጠ ውርደት እና ሞት አይመጣም::ይሄን ለመለወጥ እና የተንኮታኮተውን ክብራችንን ለማስመለስ ግን ከእያንዳንዳችን በጣም ብዙ ይጠበቅብናል:: ሌላው ወገናችን አለአግባብ ሲጠቃ:ሲታሰር:ሲበደል:ሲገደል:ሲገረፍ ስናይ እና ስንሰማ ልንናደድ ልንቆረቆር እና ልንታግል ግድ ይለናል:: አለበለዚያማ ባለቤቱ የናቀውን አሞሌ ድንጋይ ነው ብለው ይወረውሩታል የሚለው ብሂል በኢትዮጵውያን ዜጎች ላይ ይቀጥላል:: ሌላው በጣም ሊተኮርበት እና በስፋት ሊሰራበት የሚገባው ደግሞ በመላው ዐለም በሚገኙ አገራት ውስጥ በኢትዮጵያ ኤምበሲዎች የኢትዮጵያን እና የኢትዮጵውያውያንን ጥቅሞች እና መብቶች ለማስከበር ከፍተኛ የውጭ ምንዛሪ የሚከፈላቸውን ዲፕሎማቶች ግዴታቸውን በአግባቡ እየተወጡ እንደሆነ በየጊዜው መከታታል ሀላፊነታቸውን በትክክል የማይወጡትን ደግሞ ከሀላፊነታቸው እንዲነሱ በተለያየ መንገድ ግፊት ማድረግ በእነዚህ ምስኪን ኢትዮጵያውያን እህቶቻችን ላይ የሚደርሰው በደል እና ሰቆቃ ትኩረት እንዲያገኝ እና ችግሩ እንዲቀንስ ለማድረግ የሚያበረክተው አስተዋጾ ቀላል አይሆንም:: ከዚህ በተጨማሪም በውጭ አገር የሚኖረው ኢትዮጵያዊ ዘር ሀይማኖት ጾታ ሳይለይ ጉዳዩን እንደግል አጀንዳው በማየት በተለያየ መንገድ በመደራጀት በእህቶቻችን ላይ ከጊዜ ወደጊዜ እየተባባሰ በመካሄድ ላይ ያለውን ኢሰብአዊ በደል ትኩረት እንዲያገኝ ብሎም እንዲቆም እና ወንጀለኞቹም ማለትም ቀጣሪዎቹ እና ደላሎቹ ለፍርድ እንዲቀርቡ በሰላማዊ ሰልፍ: በመገናኛ ብዙሀን በሶሻል ሚዲያ ያለማሰለስ መቀስቀስ ይጠበቅብናል:: ለእኛ ችግር ከእኛ የበለጠ ማንም ሊታገልና ሊቆረቆር አይችልም::

No comments:

Post a Comment