Monday, June 4, 2012

በ2012 የስቶክሆልም ማራቶን ውድድር ኢትዮጵያውያን ሯጮች ድል ቀናቸው


ባለፈው ቅዳሜ ሰኔ 2 2004 ዓ᎐ም᎐ እዚህ ስቶክሆልም ከተማ ለ34ኛ ጊዜ በተደረገው የASICS ማራቶን ውድድር ኢትዮጵያውያን ሯጮች  ድል ቀናቸው። በሴቶች ምድብ ድርቤ ጎዳና 2 ሰዓት 40 ደቂቃ 19 ሰከንድ በማስመዝገብ አንደኛ ስትወጣ እሷን ተከትላ የገባቸው የራሺያ ተወዳዳሪ የሁለተኝነትን ደረጃ ስታስመዘግብ ሶስተኝነት በመሆን ውድድሩን ያጠናቀቀችው ደግሞ በላይነሽ ጂዳ ነበረች። በወንዶች ምድብ ደግሞ በውድድሩ  ገፍተኛ ግምት ተጥሎባቸው የነበሩት ኢትዮጵያውያን ሯጮች ደረጀ ደበሌ ቱሉ እና ሳህሌ ዋርጋ ቤቶና ሁለተኛ እና ሶስተኛ በመውጣት ውድድሩን ሲያጠናቅቁ የዮርዳኖሱ ሯጭ 2᎐19᎐16 ሰዓት በማስመዝግብ አንደኛ በመሆን  ውድድሩን አጠናቋል። እንደ ኢትዮጵያውያኑ ሁሉ በውድድሩ አዘጋጆች ከፍተኛ ግምት ተጥሎባቸው የነበሩት ኬንያውያን ሯጮች በእለቱ የነበረው እጅግ መጥፎ የአየር ሁኔታ ሊቋቋሙት ባለመቻላቸው  ምርጥ ሃያ ከሚባለው ምድብ ውስጥ እንኳን ሳይገቡ ውድድሩን አጠናቀዋል። በዚህ ዓመቱ የስቶክሆልም ማራቶን ውድድር 15᎖ 986 ከመላው ዓለም ከተወጣጡትና ውድድሩን ከጀመሩት መካከል 14᎖686ቱ ሯጮች ውድድሩን አጠናቀዋል። የዚህ ዓመቱን ማራቶን ለየት የሚያደርገው ከ84 ዓመት በኋላ በስቶክሆልም የአየር ንብረት ታሪክ በእለቱ የተመዘገበው ከፍተኛ የሆነ ብርድ፡ዝናብ እና ንፋስ ሲሆን በዚህም የተነሳ ኢትዮጵያውያኑም ሆነ ኬኒያውያን ሯጮች እንደተጠበቀው ጥሩ ውጤት ሊያስመዘገቡ አልቻሉም። 

No comments:

Post a Comment