Tuesday, October 22, 2013

እሪ በይ አገሬ መንግስታዊ ሽብር በኢትዮጵያ

የሶማሌ ክልል ልዩ ፖሊስ እና ልዩ ክፍሉ

3'12'' "የልዩ ፓሊስ አባላት እኔን እና ሌሎች ሴቶችን አስገድደው ደፈሩን።"
3'18'' "ጓደኛዬ የልዩ ፓሊስ አባላት በውሃ እና በኤሌክትሪክ ራሱን እስኪስት ካሰቃዩት በኋላ ህይወቱ አለፈች።"
3'28'' "የልዩ ፖሊስ አባላት ከ5 እስከ 10 የምንሆን እስረኞችን ነጥለው በመውሰድ ያሰቃዩን ነበር።"
ይህን በስዊድን አገር በሚገኘው ብሄራዊ የቴሌቪዥን ድርጅት ተቀናብሮ ባለፈው ሳምንት ይፋ የሆነውን ዘገባዊ ፊልም ለምን ያህ ግዜ ውስጤ እያረረ፡እየደበነ እና እየተሰቃየ እንዳየሁት በትክክል አላውቅም። ፊልሙ የተዘጋጀው ከሶማሌ ክልል በኢትዮጵያዊ አብዱላሂ ሁሴን በድብቅ ከአገር እንዲወጣ በተደረገው እና የአካባቢው ባለስልጣኖች እና የልዩ ፖሊስ አባላት በማናለብኝነት ኢሰብዓዊ በሆነ መንገድ ነዋሪውን ህዝብ  ሲያሰቃዩ  እንዲሁም በሶማሊያ ጠረፍ በኩል ወደ አካባቢው ከኦብነግ ታጣቂዎች ጋር በመግባት ዘገባ ለመስራት ሲሉ በተያዙት ሁለቱ ስዊድናውያን ጋዜጠኞች ላይ ህገወጥ ድርጊት ሲፈጽሙ በሚያሳየው ፊልም ተመስርቶ ሲሆን በዚህ ጽሁፍ መጀመሪያ ላይ እማኝነታቸውን የሰጡት እነዚህ የአካባቢው ነዋሪዎች አሁን በስደት
ኬንያ ጠረፍ በሚገኘው ደዳብ የስደተኞች ጣቢያ ይገኛሉ። ባሳለፍነው ሳምንት መጨረሻ ላይ ሂውመን ራይትስ ዎች የተባለው ዓለምዓቀፉ የሰብዓዊ መብት ተሟጋች ድርጅት አዲስ አበባ በሚገኘው የማእከላዊ ምርመራ ክፍል ፖሊስ ጋዜጠኞችን እና የተቃዋሚ ድርጅት መሪዎች፡ አባላት እና ደጋፊዎችን ኢሰብዓዊ በሆነ መንገድ በማሰቃየት እና በማንገላታት ቃላቸውን እንዲሰጡ እንደሚያደርግ የቀድሞ እስረኞችን በማነጋገር ያጠናከረውን ጥናታዊ ዘገባ ይፋ አድርጓል። ይህ ዘገባ ግን ኢትዮጵያ ውስጥ በሚገኙ የተለያዩ እስር ቤቶች እና የምርመራ ጣቢያዎች ውስጥ ታጉረው ባልሰሩት ወንጀል ቁምስቅላቸውን የሚያዩ ምህረት" ተደርጎላቸው ከእስር የሚፈቱት፡ ጉዳያቸው ፍርድቤት (ለመሆኑ ፍርድቤት የሚባለውስ ስሙ እንኳን ይታወቃል) የሚቀርበው ከፖሊስ አባላቱ በተለይም የእስርቤቱ ሃላፊ ከሆነው አብዲ ባዴ የሚቀርብላቸውን የወሲብ ጥያቄ ካሟሉ ብቻ እንደሆነ እነዚሁ የፖሊስ አባላት አፋቸውን ሞልተው በኩራት ሲናገሩ መስማት አገራችን ወዴት እያመራች እንደሆነ ለመገመት አያዳግትም። አስገድዶ መድፈር፡ ማሰቃየት እንዲያም ሲል እስረኞችን መግደል እንደተራ እለታዊ የስራ ድርሻ የሚፈጸምበት እና የሚወደስበት ጊዜ ላይ ደርሰናል። አብዛኛው ከእናቶቻቸው ጋር ታስረው የሚገኙት ህጻናት በእስርቤቱ የተወለዱ ሲሆን

አባታቸው ደግሞ የእስርቤቱ ሃላፊ እንደሆነ ይነገራል። እነዚህ ምስኪን ወገኖቻችን
ይሄን ሁሉ በደል ለውጭው ዓለም የሚያደርሱበት አንድም መንገድ የለም፡ ጡመራ፡ፌስቡክ፡ትዊተርን እርሱት። አካባቢው ለጋዜጠኞች እና ለለጋሽ ድርጅቶች ከተዘጋ ዓመታትን እያስቆጠረ ሲሆን ደፍሮ ይሄንን ድርጊት ለማጣራት እና ለማጋለጥ የሚሞክር ጋዜጠኛ የሚከፍለው ዋጋ ምን ያህል እንደሆነ ከስዊድናውያኑ ጋዜጠኞች ተሞክሮ ለመረዳት አዳጋች አይደለም።
በመቶ ሺህዎች የሚቆጠሩ ወገኖቻችን ጋር ሲነጻጸር ባህርን በማንኪያ እንደመጨለፍ ይቆጠራል። እስኪ ወደተነሳሁበት የልዩ ፓሊስ ልዩ ክፍል ልመልሳችሁ። ይህ በሱማሌ ክልል ባለስልጣናት እና በ ህውሃት የደራጀው ልዩ ፓሊስ በመባል የሚጠራው ሃይል የራሱ የሆነ እስርቤት ሲኖረው ኢትዮጵያ የፈረመቻቸውን ዓለምዓቀፍ የሰብዓዊ መብት ድንጋጊያትንም ሆነ ህገመንገስቱን በጣሰ መልኩ የፖሊስ አባላቱ የፈለጉትን እንደሚያስሩ፡እንደሚያሰቃዩ፡አስገድደው እንደሚደፍሩ እና እንደሚገድሉ ይህ በአብዱላሂ ሁሴን በድብቅ የወጣው ፊልም በግልጽ ያሳያል። እጅግ በጣም የሚገርመው ነገር እነዚህ የፖሊስ አባላት  ከክልሉ አመራር አካላት በተሰጧቸው ካሜራዎች የሚመፈጽሟቸውን ኢሰብዓዊ ድርጊቶች እንደሚቀርጹ እና ስብሰባ ላይ በጀብድ መልክ ሲናገሩ መስማት እሪ በይ አገሬ አያሰኝም ትላላችሁ። በዚህ ልዩ የሴት ታሳሪዎች ክፍል ተመርጠው እንዲገቡ የሚደረጉት ሴቶች ሲኖሩ፡ይህ ልዩ ክፍል ለምን እንደተዘጋጀ መዘርዘሩ አንባቢን ማድከም ስለሆነ ትቼዋለሁ። ስንቶቹ እህቶቻችንና እናቶቻችን
በአሁኗ ሰዓት፡ደቂቃና ሰከንድ በልዩ ፖሊስ አባላት ፍዳቸውን እንደሚያዩ ያች ልዩ ክፍል ትፍረድ።

የመንግስት ሹመኛ ወይስ ፊልም አቀነባባሪ
የአቶ አብዱላሁ ወረር ጀብዱ በዚህ ብቻ አያበቃም ዩዋን ፐርሹን የተባለው ስዊድናዊ ጋዜጠኛ ከመከላከያ ሰራዊት በተተኮሰ ጥይት እጁ ደህንነት ተመቶ ህክምና በአስቸኳይ ማግኘት ሲገባው ቁስሉ እንዲያመርቅዝ እና እንዲበከል በማድረግ በፊልሙ ቀረጻ እንዲሳተፍ ከፍተኛ አስተዋጽኦ በማድረግ ሰብዓዊ እና ዜግኔታዊ ግዴታቸውን በመወጣት የልማት አርበኝነታቸውን አስመስክረዋል። በኔ በኩል ኢትዮጵያ እንደ እኝህ ያለ ባለራእይ እና ለሰብዓዊ መብት ተቆርቋሪ መሪ ተፈጥሮባት አያቅም ወደፊትም የሚፈጠር አይመስለኝም። የኢትዮጵያን መልካም ገጽታ እና ስም በዚህ መልኩ ለማሳየት የሚደረገው ጥረት ሁላችንም የበኩላችንን ርብርብ ማድረግ ይጠበቅብናል። ግን፡ግን   ከስዊድናውያኑ ጋር ፊቱ ሁሉ ጥርስ በጥርስ ሆኖ ጮቤ እየረገጠ በኢትዮጵያ የመከላከያ ሰራዊት ተማረከ የተባለው የኦብነግ ምርኮኛ ኢትዮጵያን በድንቃ ድንቅ መዝገብ ላይ በማስመዝገቡ ሊሸለም አይገባውም ትላላችሁ። እነዚህ ፊልም አቀነባባሪ የመንግስት ሹመኞች በዚህ መልኩ ከቀጠሉ ሆሊውድ ከአሜሪካን ጠቅልሎ ወደ ኢትዮጵያ እንደሚገባ እና ታዋቂው የፊልም አቀነባባሪ ስቲቨን ሲፒልበርግ ከስራ ውጭ እንዳይሆን ትልቅ ስጋት አለ።
እና ሰላም ለማስጠበቅ እንዲሁም ከችግር እና ከበሽታ እንዲወጡ ለማድረግ የማይፈነቅለው ድንጋይ የለም። ከእነዚህ ሁሉን አቀፍ ጥረቶች አንዱ ሹመኞቹ ውስጣቸው ያለውን ኪነጥበባዊ ክህሎት እንዲያወጡት እና ለተጠቃሚ ህብረተሰብ ግልጋሎት እንዲያውሉት ከማረታት በተጨማሪ በቀረጥ ከፋዩ ገንዘብ የተገዙ ውድ ካሜራዎችን በመጠቀም የሚፈጽሟቸውን ልማታዊ የማሰቃያ መንገዶች ለዚሁ ሲባል በተገነቡት የብዝኋን መገናኛ ተቋማት እንዲያስተላልፉ እንዲያም ሲል በአሸባሪነት እና አሸባሪነትን በመደገፍ በተከሰሱ ሰዎች ላይ በማቀነባበር ፊልሙ በማስረጃነት በፍርድ ቤት እንዲቀርብ ያላሰለሰ ጥረት በማድረግ ላይ ይገኛል። ለዚህ እንደአብነት የሚያገለግለን ደግሞ ሁለቱ ስዊድናውያን ጋዜጠኞች እንዲሳተፉበት የተደረገው እና በክልሉ ምክትል ፕሬዚዳንት አብዱላሂ ወረር በተደጋጋሚ እንዲቀረጽ ከተደረገ በኋላ በዋናው ፕሬዝደንት አዎንታዊ ምላሽ በማግኘት ለሟቹ ጠቅላይ ሚኒስትር ፍርድቤት በማስረጃነት በማቅረብ ጋዜጠኞቹ ሽብርተኝነትን በመደገፍ ክስ ተወንጅለው 11ዓመት ተፈርዶባቸው ዘብጥያ እንዲወርዱ በማድረግ በሚሊዮን የሚቆጠሩ ወገኖቻችን ያለስጋት እና ፍርሃት በሰላም እዲኖሩ አስችለዋል።
ፌደራሊዝም እና ሚጢጢ አምባገነኖቻችን
ፌዴራሊዝም ምን ያስታውሰኛል ብትሉ በሰማኒያዎች ሲደረግ የነበረው በወቅቱ ብወዛ በመባል ይታወቅ የነበረው የሲቪል ሰርቪስ ማሻሻያ ፕሮግራም፡፡ በወቅቱ ጋምቤላ በመምህርነት አገለግል የነበር ሲሆን ክልሎች በጀት ተመድቦላቸው ራሳቸውን በራሳቸው እንዲያስተዳድሩ በሚል የተለያዩ መንግስታዊ ተቋማትና አገልግሎት ሰጪዎች በጥድፊያ ሰራተኛ የሚቀጥሩበት እና ሃላፊዎች የሚሾሙበት ነበር። ብዛት ያላቸው አብረውኝ በመምህርነት ሲያገለግሉ የነበሩ ግለሰቦች በአንድ ምሽት የእነዚህ ትላልቅ መንግስታዊ ተቋማት ሃላፊዎች ሆነው አገኘሁዋቸው። ልብ አድርጉ እነዚህን ከፍተኛ የሆነ የትምህርት እና የስራ ልምድ የሚጠይቁ ቦታዎች ላይ በሃላፊነት የተቀመጡት ከሙያው ጋርም ሆነ ከሃላፊነቱ ጋር ምንም ዝምድና የሌላቸው ግለሰቦች ነበሩ። በጣም የሚያሳዝነው እና የሚገርመው ግን አብዛኛዎቹ እነዚህ ሹመኞች በስነስርዓት ጉድለት ማህደራቸው የተበላሸ፡ በአልክሆል
መጠጦች እና ሌሎች ሱሶች የተጠመዱ፡ ሴት ተማሪዎችን በማባለግ የታወቁ ከዛም አልፎ ተርፎ ለአካባቢው ህብረተሰብ የመጣውን የእርዳታ እህል ሲሸጡ በፖሊስ እጅ ከፍንጅ የተያዙ ይገኙበታል። ጉዳዩ በዚህ ቢያበቃ ጥሩ ነበር፡ጭራሽ ይባስ ብሎ ተማሪዎቻችንም ትምህርታቸውን እያቋረጡ ሹመኞች ሆነው ቁጭ አሉ። ከዛማ ምኑ ቅጡ አካባቢውን ከድህነት እና ከበሽታ ለማላቀቅ ከለጋሽ ድርጅቶችም ሆነ ከግብር ከፋዩ ህብረተሰብ የሚላከው ገንዘብ በመቶ ሺህ የሚቆጠር ዋጋ ለሚያወጡ ላንድክሩዘር እና ኮብራ መግዥያ ሲውል ቀሪው ደግሞ ሙሉ ሱፍ ልብስ (አስቡት በዚያ እንደ እሳት በሚለበልብ ጸሃይ ሱፍ ልብስ ከነከረባት) ለመግዛት እና ማታ ማታ አስረሽ ምቺው ይባልበት ነበር። የአካባቢው ተወላጅ ወይም የህውሃት ቀንደኛ ደጋፊ መሆን ዋና መስፈርቶች ነበሩ። ባቋራጭ ድህነት ደህና ሰንብች፡ የምን ቾክ ማቡነን፡ የምን ሞዴል ስድስት። የምታስታውሱ ካላችሁ ይህንን ጉዳይ በተመለከተ ባለራዕዩ መሪያችን ጥያቄ ቀርቦላቸው ሲመልሱ ባለስልጣኖቹ አለመማራቸው ወይም የስራ ልምድ እጥረታቸው አማካሪዎችን በመመደብ ሊቃለል እንደሚችል ተናግረዋል። ዛሬ እንግዲህ በመላው አገሪቱ በሚገኙ
የተለያዩ አካባቢዎች ህዝቡን እንዲገዙ የተመረጡት ሰዎች ታሪክ ይህን የሚመስል ሲሆን የሶማሌ ክልልም ከእነዚህ የተለየ አይደለም። አብዛኛዎቻችን እንደተራ ነገር የምንቆጥረው ለሰው ልጅ መሰረታዊ ከሆኑት ነገሮች የሆነው ውሃ በእነዚህ ሚጢጢ አምባገነኖች በመሳሪያነት በመጠጥ ውሃ የሚሰቃየውን ህዝብ እና ከብቶቹን ለማሰቃየት ሲውል ማየት እጅግ ህሊናን የሚነካ ነው። እነዚህ ሚጢጢ አምባገነኖች የሚኖሩት በከፍተኛ ወጭ በተገነቡ ከእብነበረድ በተሰሩ ቤቶች ሲሆን በመንግስት ወጭ እጅግ ውድ መኪኖች፡ ሾፌር እና ጠባቂ ተመድቦላቸው ከቦታ ቦታ የሚንቀሳቀሱ ሲሆን ለህዝብ አገልግሎት ተብሎ የተገነቡ የውሃ፡የመብራት እና የጤና ተቋማት የእነሱን መልካም ፍቃድ ካላገኘ አይከፈትም። እዛ ውድ መኪና ውስጥ፡ የኋላው ወንበር ላይ ከቆንጃጅት ጋር በመሆን ለጋ የአወዳይ ጫት በታሸገ ውሃ ካልሆነም በቢራ እያወራረዱ በየመንገዱ ዳር ላይ በተቀለሱ ሊወድቁ አንድ ሃሙስ የቀራቸው ጎጆዎች ላይ አቧራ እያቦነኑ ከመሄድ የበለጠ ምን የሚያስደስት ነገር አለ? ከዛም በጠባቂዎች በመታጀብ ከዚህ በፊት ተመርቆ የተዘጋ እና እንደገና እንደአዲስ የሚመረቅ የውሃ መስጫ ፊትለፊት በመሆን በውሃ ጥም የሚሰቃየውን ምስኪን ህዝብ ምስጋና እንዲያቀርብ ማሰገደድማ ነፍስን ሃሴት ውስጥ ነው የሚከታት። በተለይ በተለይ እነዛ ተርበው፡ተጠምተው፡ታርዝው ፊታቸው በዝንብ ተወሮ ሆዳቸው ተቆዝሮ ባዶ እግራቸውን በመሆን በፈራ ተባ ይህን ከዚህ በፊት አይተውት የማያውቁትን የታሸገ ውሃ ለመቅመስ ተሰልፈው ማየት ለእነዚህ ሚጢጢ አምባገነኖች ከፍተኛ የመንፈስ እርካታ የሚሰጣቸው ነገር ነው። የኢትዮጵያ ፌደራሊዝም በከፋፍለህ ግዛ መርህ ህውሃት ስልጣን ላይ ለመቆየት እና አገሪቱን እንዳሻው ለመዝረፍ በአምሳሉ የፈጠራቸው፡ ህዝባቸውን ለማሰቃየት እና ለማንገላታት የሚሰጣቸውን ትዕዛዝ ለመፈጸም ቅንጣት ያማያወላውሉ የሆድ አደሮች እና የጥቅመኞች ስብስብ እንጂ ሌላ ምንም ሊባል አይችልም።            
እንደማጠቃለያ አብዱላሂ ሁሴን ከኢትዮጵያ በድብቅ ያስወጣቸውን እነዚህን የልዩ ፖሊስ አባላት እና የክልሉ ባለስልጣናት በነዋሪው ህዝብ ላይ ኢሰብዓዊ ወንጀሎች ሲፈጽሙ የሚያሳየውን ቪድዮ ስዊድን አገር ለሚገኘው የጦር ፍርድቤት ያስረከበ ሲሆን ጉዳዩ በዓለም ዓቀፉ የወንጀለኞች ፍርድቤት እንደሚታይ ይጠበቃል። እነ አቶ ደሳለኝ ሃይለማርያም እና ባልደረቦቻቸው አፍሪካውያን አምባገነኖች በህዝባቸው ላይ ለፈጸሙት እና እየፈጸሙ ላለው ወንጀሎች በአለምዓቀፉ የወንጀለኞች ፍርድቤት እንዳይታይ የሚያደርጉት ጉንጭ አልፋ ክርክር እና ጩኀት ነግ በኔ በሚል ራሳቸውን ለማዳን የሚደረግ ከንቱ መፍጨርጨር መሆኑ ዛሬ የአደባባይ ምስጢር ነው።

No comments:

Post a Comment